የኢትዮጵያ መግሥት በዶ.ር ደብረ ጽዮን የሚመራው የህወሓት ቡድን የፕሪቶሪያውን ስምምነት ጥሷል ማለቱን የሀገር ውስጥ ብዙኅን መገናኛ ዘገቡ።
የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት፣ በክልሉ ወቅታዊ ጉዳይ ላይ አዲስ አበባ ለሚገኙ ዲፕሎማቶች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በማብራሪያቸው፣ ለፕሪቶሪያው ስምምነት መተግበር የዓለም አቀፉን ማኅበረሰብ ድጋፍ መጠየቃቸውን የመንግሥት ብዙኅን መገናኛዎቹ ዘግበዋል፡፡
በዶ/ር ደብረ ጽዮን የሚመራው ቡድን ስምምነቱን ጥሷል መባሉን ማስተባበሉን በማስተባበል፣ በአንጻሩ ስምምነቱ የተጣሰው በእነ አቶ ጌታቸው ረዳ ቡድን ነው ሲል በተደጋጋሚ ምላሽ መስጠቱ ይታወቃል፡፡ በሌላ በኩል የአፍሪካ ኅብረት፣ በክልሉ ባለው ውጥረት ተሳታፊ የሆኑ አካላት ራሳቸውን እንዲያቅቡና ችግሩ በውይይት እንዲፈታ ጠይቋል፡፡
በህወሓት የፖለቲካ አንጃዎች መካከል በተፈጠረው ሽኩቻ እጇ እንዳለበት በአቶ ጌታቸው የተከሰሰው የኤርትራ መንግሥት ክሱን አስተባብሏል።
የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት፣ በክልሉ ወቅታዊ ጉዳይ ላይ በአዲስ አበባ ለሚገኙ ዲፕሎማቶች ማብራሪያ መስጠታቸውን ጠቅሶ የዘገበው ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት፣ በውይይቱ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ራሱን ነጥሎ የወጣው የህወሓት አንጃ የፕሪቶሪያው ስምምነት ሙሉ ለሙሉ እንዳይተገበር እንቅፋት ኾኗል ማለታቸውን ዘግቧል።
በህወሓት አመራሮች መካከል አለመግባባቱ ከተካረረ ወዲህ በፌደራል መንግሥቱ በኩል እንዲህ ዐይነት አቋም ሲያዝ የመጀመሪያው ነው።
የትግራይ ክልል ሰሞናዊው ውጥረት ከተከሰተ በኋላ፣ በአዲስ አበባ ላሉ ዲፕሎማቶች ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ መንግሥት በተሰጠ በዚኽ ማብራሪያ ላይ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም በክልሉ የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርግም ዶ/ር ጌዲዮን ጥሪ ማድረጋቸውን ከፎቶግራፎች እና ከቪዲዮ ጋራ የወጣው ዘገባ አመልክቷል፡፡
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት ጌታቸው ረዳም፣ በክልሉ ላለው ውጥረት፣ “መፈንቅለ መንግሥት እያደረገ ነው” ያሉትን እና “አንድ የህወሓት አንጃ” ሲሉ የጠቀሱትን አካል ተጠያቂ በማድረግ በትላንትናው ዕለት ለጋዜጠኖች ከሰጡት ማብራሪያ ጋራ ተመሳሳይ ይዘት ያለው ማብራሪያ ለዲፕሎማቶች መስጠታቸው በዘገባው ተመልክቷል፡፡
በዶክተር ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል የሚመራው ህወሓት ምክትል ሊቀ መንበር የኾኑት አቶ ዐማኑኤል አሰፋ በበኩላቸው፣ ትላንት ማምሻውን ለብዙኀን መገናኛ በሰጡት መግለጫ፣ በአኹኑ ጊዜ በትግራይ ክልል እየተካሔደ ያለው፣ “በወረዳዎች እና በከተሞች የሕገ መንግሥት ማስከበር እንጂ፣ መፈንቅለ መንግሥት ተብሎ እየተገለጸ ያለው ስሕተት ነው፤” ሲሉ ክሱን ተከላክለዋል፡፡
“በትግራይ ክልል በአሁኑ ጊዜ አዲስ የተለየ ክስተት ሳይኖር በወሬ ግርግር እንደተፈጠረ እየተገለፀ ነው ያለው” ሲሉም ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል የአፍሪካ ኅብረት፣ በህወሓት ውስጥ የተፈጠረውን ሁኔታ በጥልቅ ስጋት በቅርበት እየተከታተለ መሆኑን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ኅብረቱ በመግለጫው፣ “በአሁኑ ወቅት እየታዩ ካሉት ሁኔታዎች በመነሳት ወገኖቹ በህወሀት እና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከል ፕሪቶሪያ ላይ በተፈረመው ግጭቶችን በዘላቂነት የማቆም ስምምነት የተካተቱትን ግዴታዎች እንዲያከብሩ እናበረታታለን ብሏል።
ስምምነቱን ማክበር በብዙ ፈተና የተገኘው ሰላም እንዲዘልቅ ብሎም ለዘላቂ ሰላም ግንባታ፥ ለዕርቅ እና ለልማት አመቺ ሁኔታ ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን አጽንዖት ሰጥተን እናሳስባለን ያለው የአፍሪካ ኅብረት ሁሉም ባለድርሻ አካላት የገቧቸውን ቃሎች እንዲያከብሩ እና ሰላማዊ መፍትሄ እንዲገኝ በትብብር እንዲሰሩ እንማጸናለን ብሏል።
የአፍሪካ ኅብረት ለፕሪቶሪያ ስምምነት ተግባራዊነት የማያወላውል ድጋፉን በድጋሚ ያረጋግጣል፥ በዚህ ሂደትም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር አብሮነቱን ይቀጥላል ያለው መግለጫው ኅብረቱ በከፍተኛ ልዑክ አማካይነት በወገኖቹ መካከል ውይይት እና ትብብር የሚኖርበትን መንገድ ማመቻቸቱን ለመቀጠል ዝግጁ መሆኑን አስታውቋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የዩናይትድ ስቴትስ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ከፍተኛ አባል ሴናተር ጂን ሻሂን በኤክስ ገጽ ባሰፈሩት ጽሑፍ በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል እየተባባሰ ያለው ውጥረት እንዳሳሰባቸው ገልጸዋል።
“ከግጭት እና አለመረጋጋት ይልቅ ለሰላም እና ለዲፕሎማሲ ትኩረት ሊሰጥ ይገባል” ያሉት ሴናተር ሻሂን፣ “መሪዎቹ የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነትን እንዲያከብሩ ጥሪ አቀርባለሁ” ብለዋል፥ አስከትለውም በአፍሪካ ቀንድ የሚፈጠር ግጭት “በቀጣናው የባሰ ስቃይ ከማስከተል ያለፈ ውጤት አይኖረውም” ብለዋል። የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት ጌታቸው ረዳ፣ “ከኤርትራ ጋር ግንኙነት እየፈጠሩ ያሉ አካላት አሉ” ሲሉ ወንጅለው ነበር፡፡
በሌላ በኩል የኤርትራ የማስታወቂያ አቶ የማነ ገብረ መስቀል ትላንት በኤክስ ላይ ባወጡት መግለጫ፣ “ኤርትራ በህወሓት የፖለቲካ አንጃዎች ውስጥ የተፈጠረውን የውስጥ ሽኩቻ የማባባስ ፍላጎት የላትም ፤ ይህ በትግራይ ህዝብ ላይ አላስፈላጊ ስቃይ ያስከትላል ብላ ታምናለች” ብለዋል።
በዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል በሚመራ ህወሓት ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት አቶ ዐማኑኤል አሰፋም ትላንት በሰጡት መግለጫ፣ ከኤርትራ መንግስት ጋራ ሌላ አካልን ለመጉዳት ተብሎ የሚፈፀም ግንኙነት የለንም በማለት የአቶ ጌታቸውን ክስ ተከላክለዋል።
የኤርትራው ማስታወቂያ ሚኒስትር አቶ የማነ በትላንቱ የኤክስ መግለጫቸው “የኤርትራ ጦር በኢትዮጵያ ትግራይ ክልል አለ” በሚል በተወሰኑ አካላት የሚሰነዘረው ተደጋጋሚ ክስ “ፍፁም ሀሰት እና ግጭት ለመቀስቀስ ምክንያት ለመፍጠር የሚደረግ ነው” ሲሉ ገልፀዋል፡፡
“ኤርትራ የፕሪቶሪያን የሰላም ስምምነት ለማፍረስ ምንም ፍላጎት የላትም። ይህ በመሰረቱ የኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ነው” ያሉት አቶ የማነ “በቀይ ባህር ዙሪያ በተለያዩ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሃይሎች ሌት ተቀን የሚያወጧቸው ግጭት ቀስቃሽ መግለጫዎች ለአላስፈላጊ ውጥረት ምንጭ ሆነው ቀጥለዋል” በማለት ከሰዋል፡፡
በትግራይ ክልል ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ እና የኤርትራን ክስ በተመለከተ ከኢትዮጵያ መንግሥት በኩል አስተያየት ለማግኘት ያደረግነው ጥረት ለአሁን አልተሳካም፡፡
Crédito: Link de origem